የአማራ መንገድ ሥራዎች ድርጅት አመራሮችና ሰራተኞች በህልዉና ዘመቻው እየተዋደቀ ለሚገኘዉ የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የአማራ እና የሌሎች ክልሎች ልዩ ሀይል፣ ለፋኖ እና ለሚሊሺያ አባላት ደማቸዉን ለገሱ፣

በሽብርተኝነት የተፈረጀው ትህነግ (የትግራይ ህዝብ ነጻ-አውጪ ግንባር) የኢትዮጵያን ዉድቀት ለሚመኙ አንዳንድ የዉጭ ሀገራት ቅጥረኛ በመሆን በክልላችን እና በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች በአስነዋሪ ተግባር ታጅቦ የከፈተውን የሀገር ክህደት፣ የባንዳነት ተግባር እና ጥቃት ለመመከት ሁሉም አካላት የበኩላቸውን ድጋፍ እንዲያደርጉ መንግስት ጥሪ ማቅረቡ ይታወቃል፡፡
በዚህም መሰረት የአማራ መንገድ ሥራዎች ድርጅት አመራሮችና ሰራተኞችም የክልላችን መንግስት ያቀረበውን ጥሪ በመቀበል የአንድ ወር ሙሉ ደመወዛቸውን ወይም መቶ ፐርሰንት ለህልውና ማስከበር ዘመቻው የወሰኑ ሲሆን አማራ መንገድ ሥራዎች ድርጅትም እንደ ተቋም ለክልሉ ህዝብና ለሀገር የምሰስተዉ የለኝም በማለት ለህልዉና ማስከበር ዘመቻዉ ማሳኪያ 20,000,000.00 (ሀያ ሚሊዮን ብር) ለመሥጠት ቃል በመግባት የህዝብና የሀገር አለኝታ መሆኑን አረጋግጧል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ የድርጅቱ አመራርና ሰራተኞች በራሳቸዉ አነሳሽነት በህልውና ዘመቻው እየተሳተፉ ለሚገኙት የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የአማራ እና የሌሎች ክልሎች ልዩ ሀይል፣ ለፋኖ እና ለሚሊሺያ አባላት በትናንትናዉ ዕለት ማለትም በ19/12/2013 ዓም በድርጅቱ ቅጥር ግቢ በተዘጋጀዉ ፕሮግራም በመገኘት ደሜን ለወገኔ፣ ደሜን ለሀገሬ በሚል ትልቅ ስሜት ደማቸዉን ለግሰዋል፡፡