ማኔጅመንት አባላት ድርጅታችን እየገነባቸው የሚገኙ ፕሮጀክቶችን ጎበኙ

ማኔጅመንት አባላት ድርጅታችን እየገነባቸው የሚገኙ ፕሮጀክቶችን ጎበኙ
የድርጅታችን የሥራ አመራር ቦርድ አባላት እና የአብክመ ገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ማኔጅመንት አባላት ድርጅታችን እየገነባቸው የሚገኙ ፕሮጀክቶችን ጎበኙ።

የአማራ መንገድ ሥራዎች ድርጅት የቦርድ አባላት፣ የአማራ ክልል ገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ሃላፊዎች እና የማኔጅመንት አባላት የዳንግላ ጃዊ የጠጠር መንገድ ሥራ እና የቡሬ የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ አስፓልት መንገድ ሥራ ፕሮጀክቶችን ጎበኙ፡፡ በጉብኝቱ ድርጅታችን ሲመሰረት መስራች አመራር የነበሩትና በአሁኑ ወቅት የድርጅቱ የሥራ አመራር ቦርድ አባል የሆኑት አቶ ስማቸው ንጋቱ፣ የአብክመ የገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ዋና እና ምክትል ሃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡

የቡሬ የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ አስፓልት መንገድ ስራ ፕሮጀክት ተወካይ ሃላፊ አቶ ታረቀኝ ተስፋየ እና ከፍተኛ የሆነ የአለት ቆረጣ ያለበት የዳንግላ ጃዊ ጠጠር መንገድ ስራ ፕሮጀክት ሃላፊ አቶ ከተማው ምኑየ ፕሮጀክቶቹ የሚገኙበትን የአፈፃፀም ደረጃ ለጎብኝዎች አብራርተዋል፡፡

የድርጅታችን ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ አስማማው አለማየሁ በበኩላቸው ድርጅቱ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ አሁን እስካለበት ጊዜ ያለውን የገቢ፣ የካፒታልና የአትራፊነት ደረጃን እና የመፈፀም አቅምን የሚያሳይ ገለፃ ለጎብኝዎቹ አቅርበዋል።

ለድርጅቱ መመስረት ትልቅ አስተዋፅኦ የነበራቸው የቀድሞው የገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ሀላፊ እና የአሁኑ የአመሥድ የስራ አመራር ቦርድ አባል አቶ ስማቸው ንጋቱ ድርጅቱ በአነስተኛ ካፒታል፣ ማሽን እና የሰው ሃይል ተመሰርቶ በሃገር በቀል ኮንትራክተር ይገነባል ተብሎ የማይታሰበውንና እስከ የ70 ሜትር አለት ቆረጣ የሚጠይቀውን የዳንግላ ጃዊ ጠጠር መንገድ ስራ ፕሮጀክት እና እጅግ ውስብስብ የሆነውን እንዲሁም አዲሰ ቴክኖሎጅ ተግባራዊ የተደረገበትን የቡሬ የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ አስፓልት መንገድ ሥራ ገንብቶ ከዚህ ደረጃ ላይ ማድረስ መቻሉ እንደ ክልል ብሎም እንደ ሃገር የሚያኮራ እና ትልቅ አቅም ነው ብለዋል፡፡

በጉብኝቱ የተሳተፉት ሌሎች የድርጅታችን የቦርድ አባላት እንዲሁም የአብክመ የገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ሃላፊዎች እና የማኔጅመንት አባላት አማራ መንገድ ሥራዎች ድርጅት አስቸጋሪ የሆነ መልክዓ ምድር ባላቸው ቦታዎች ገብቶ ጥራቱን የጠበቀ መንገድ በመስራቱ እንዲሁም በውጭ ሀገር የግንባታ ተቋራጮች ተወስኖ የቆየውን የአስፓልት መንገድ ስራ በዚህ ደረጃ እየፈፀመ በማየታቸው ደስተኛ መሆናቸውን እና ለክልላችን ህዝብ ትልቅ አቅም እንደሚሆን ተናግረዋል።

በመጨረሻም የገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ሃላፊዎች እና የማኔጅመንት አባላት ድርጅቱ ከዚህ በላይ የክልሉ ትልቅ አቅም ሆኖ እንዲቀጥል አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ ለማድረግ እና በጋራ ተደጋግፎ ለመዝለቅ ግንኙነታቸው ከመቸውም ጊዜ በላይ ተጠናክሮ ይቀጥላል በማለት ገልፀዋል።