ኮርፖሬሽናችን ከ672 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ በማድረግ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥሯል። አቶ መብት አድማስ የኅብር ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ

yesra edil
ኅብር ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን የላቀ ለውጥ እና ሁለንተናዊ ከፍታ ላይ ለመድረስ የሚያስችለውን የአደረጃጀት፣ የስያሜ እና የሎጎ ለውጥ ማድረጉ የካቲት 13/ 2017 ዓ.ም በተካሄደው የማስተዋወቅ እና ስራ ማስጀመሪያ መርሀ-ግብር ተገልጿል። በመርሀ ግብሩ ንግግር ያደረጉት ዋና ስራ አስፈጻሚው ኮርፖሬሽኑ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ አካባቢዎች በርካታ የጠጠር እና የአስፓልት መንገድ፣ ድልድዮች፣ ትምህርት ቤቶች፣ ሆስፒታሎች እና ሌሎች ግንባታዎችን መሥራቱን ተናግረዋል።

ኅብር ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን በአሁኑ ጊዜ ከ13 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን ፕሮጀክቶች ውል ወስዶ በግንባታ ሥራ ላይ እንደሚገኝም ተናግረዋል። የባሕር ዳር ኮሪደር ልማትንም ውል ወስዶ እየሠራ መኾኑን ጠቅሰዋል። በቀጣይም ሌሎች ትላልቅ የመንገድ ፕሮጀክቶችንም ለመሥራት በዝግጅት ላይ መኾኑን ገልጸዋል።

ማህበራዊ ኃላፊነትን ከመወጣት አንጻር ኅብር ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን ከ5.6 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጭ ትምህርት ቤት ገንብቶ ማስረከቡን፣ ከ2 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ በማድረግ ለአቅመ ደካሞችን ቤት ጥገና ማድረጉን፣ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚኖሩ ወገኖች የጤና መድኅን ሽፋን መስጠቱን፣ ከ11 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጭ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽ/ቤት ግቢ አስፓልትን የገነባ መሆኑን የገለጹት ዋና ስራ አስፈጻሚው ከ672 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ በማድረግም ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩንም ገልጸዋል።