ኮርፖሬሽኑ ለወራቤ ቦዥባር አስፋልት መንገድ ስራ ፕሮጀክት የገዛው አዲስ አስፋልት ፕላንት በሚቀጥለው ሳምንት አስፓልት ለማምረት ዝግጁ መሆኑ ተገለፀ።

plant
ኮርፖሬሽኑ ለወራቤ ቦዥባር አስፋልት መንገድ ስራ ፕሮጀክት ዘመናዊ እና ትልቅ የማምረት አቅም ያለው አዲስ አስፋልት ፕላንት ግዥ በመፈጸም ለስራ ዝግጁ ማድረጉን የፕሮጀክቱ ኃላፊ አቶ እንዳለው ደጉ ገልጸዋል። የወራቤ ቦዥባር አስፋልት መንገድ ፕሮጀክት የአካባቢው ማህበረሰብ በጉጉት የሚጠብቀው ፕሮጀክት እንደመሆኑ መጠን ከፍተኛ ትኩረት የምንሰጠው ፕሮጀክት ነው ያሉት ኃላፊው ኮርፖሬሽኑ ባለፉት ዓመታት ይጠቀምበት የነበረው የኪራይ አስፋልት ማቅለጫ ማሽን ስራው የሚፈልገውን ምርት የማምረት አቅም ያልነበረው በመሆኑ በፕሮጀክቱ አፈጻጸም ላይ የራሱን አሉታዊ ተጽዕኖ አሳድሯል ሲሉ ገልጸዋል።

ኮርፖሬሽኑ የፕሮጀክቱን አፈጻጸም በገመገመበት ወቅት ፕሮጀክቱን በፍጥነት ለማጠናቀቅ የተሻለ የማምረት አቅም ያላቸው የድንጋይ ወፍጮ እና አስፋልት ማቅለጫ ማሽኖች ማስገባት አስፈላጊነት ላይ በመግባባት እርምጃ ወስዷል ሲሉ ፕሮጀክት ኃላፊው አስታውቀዋል። በዚህም መሰረት አንድ ተንቀሳቃሽ የድንጋይ ወፍጮ ቀድሞ ገብቶ በማምረት ላይ ይገኛል ያሉት ፕሮጀክት ኃላፊው የአስፋልት ማቅለጫ ማሽኑ ደግሞ የተከላ ሂደቱን አጠናቆ ለስራ ዝግጁ ሆኗል ሲሉ አስረድተዋል። እነዚህ ማሽኖች ፕሮጀክቱን በፍጥነት ለማጠናቀቅ ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ወሳኝ ማሽኖች ናቸው ሲሉ ተናግረዋል።

በተያያዘም የፕሮጀክቱ የፕላንት እና ማምረቻ ክፍል ቴክኒካል ቡድን መሪ አቶ ዮናስ ሙሉጌታ በበኩላቸው ማሽኑ ዘመናዊ እና ትልቅ የማምረት አቅም ያለው መሆኑን ገልጸው የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት የካሊብሬሽን ስራ ተሰርቶ ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ አስፋልት ማምረት የሚያችለው ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተረጋግጧል ሲሉ ገልጸዋል።

ፕላንቱ በሰዓት 120 ቶን አስፋልት ማምረት እንደሚችል እና እንደአስፈላጊነቱ አውቶማቲክ፣ ሴሚ አውቶማቲክ እንዲሁም ማኑዋል የመቆጣጠሪያ ሲስተም ያለው እንደሆነ አቶ ዮናስ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በተጨማሪም በቀን እስከ አንድ ኪሎሜትር ለማንጠፍ የሚያስችል አስፋልት የማምረት አቅም ያለው ፕላንት እንደሆነ አቶ ዮናስ ጨምረው ገልጸዋል።
plant